(በዘሪሁን ሙሉጌታ)

ባለፉት ሁለት ሳምንታት በሺህ የሚቆጠሩ የአማራ ክልል ተወላጆች ከቤንሻንጉል ክልል ተፈናቅለው በጎጃም ፍኖተሰላም አካባቢ እንዲሰፍሩ የተደረገው በስህተት መሆኑን የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ገለፁ። የተፈናቀሉት በሙሉ ቀደም ሲል ወደነበሩበት እንዲመለሱ መወሰኑንም አስታወቁ።

የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አህመድ ናስር በተለይ ለሰንደቅ ጋዜጣ እንደገለፁት ሰሞኑን ከክልሉ እንዲፈናቀሉ የተደረጉ የአማራ ተወላጆች በሙሉ እንዲመለሱ መወሰኑን ገልፀዋል።

Citizens evicted from Benshangul region ina shelter in Fenote-Selam [Photo - Addis Admass]
Evicted citizens in a shelter in Fenot-Selam last week [Photo: Addis Admas]

በክልሉ ከአማራ ክልል ብቻ ሳይሆን ከኦሮምያ ከመሬት ጥበት፣ ከአፈር ምርታማነት ማጣት ጋር በተያያዘ የተሻለ መሬት ፍለጋ ሰዎች ወደ ክልሉ እንደሚገቡ የገለፁት አቶ አህመድ ነገር ግን ሰፈራው በሕገ-ወጥ መንገድ ሲፈፀም መቆየቱን አስታውሰዋል።

“እኛ የምንቃወመው በሕገ-ወጥ መንገድ በደን ውስጥ እየገቡ ደን እየመነጠሩ ሰፈራ ማስፋፋቱን ነው። ይህ ደግሞ ለክልሉ ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገርም አደጋ አለው” ያሉት አቶ አህመድ“በሕገ-መንግስታችን መሠረት ማንኛውም ሰው ለስራ ቢዘዋወር ችግር የለውም” ብለዋል።

ነገር ግን አሁን ከክልሉ እንዲፈናቀሉ የተደረጉት ለምን እንደሆነ ርዕሰ መስተዳደሩ ተጠይቀው ከታች ያለው አስተዳደር ስህተት በመፈፀሙ ነው ሲሉ አምነዋል። አስተዳዳሪዎቹ ሕዝቡን ያፈናቀሉት ሕገ-ወጥ ሰፈራውን ከነባሩ የመለየት ስራ ላይ ተናቦ የመስራት ችግር በማጋጠሙ ነው ብለዋል።

“አስተዳደራችን አካባቢ ስህተት ተፈፅሟል። መፈፀም ግን አልነበረበትም። ነገር ግን እንደ ክልል መንግስት በሕገ-ወጥ መንገድ የሰፈሩትን መቆጣጠር አለብን። ኅብረተሰቡ በፈለገው ጊዜና ወቅት እየተነሳ ደን እየመነጠረ መስፈር አስቸጋሪ ስለሆነ ስርዓት መያዝ አለበት የሚል አቋም አለን” ያሉት አቶ አህመድ ስህተት የፈፀሙ የአስተደደር አካላት ላይም ግምገማ በማካሄድ ማስተካከያ እናደርጋለን ብለዋል።

በጉዳዩ ላይ ከአማራ ክልል ባለስልጣናት ጋር ምክክር መደረጉንም ያስታወሱት አቶ አህመድ ችግሩ በድጋሚ ሊፈጠር የማይችልባቸውን ቀዳዳዎች ለመድፈን ከአማራ ክልል መንግሥት ጋር ስምምነት ላይ መደረሱንም ተናግረዋል።

እስካሁን ባለው ሁኔታ ወደ 1 ሺህ 346 አባወራዎች ከ3ሺህ ቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲፈናቀሉ መደረጉን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ ችግሩ ከኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት ጋር የተያያዘ መሆኑንም አስረድተዋል።

“በክልላችን አንዳንድ ቦታዎች ሰዎቹን ወደ አካባቢው ካስገቡአቸው በኋላ የሚታይ ችግር አለ። በተለይ ከመሬት አስተዳደር ጋር በተያያዘ ችግር አለብን። በየጊዜው እናጣራለን፤ እንጠርጋለን፣ እንገመግማለን ችግሩን ግን ሙሉ በሙሉ ማፅዳት አልተቻለም” ሲሉ ተናግረዋል።

ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወደ ክልሉ መግባትና መውጣት የሚያስችል ሕገ-መንግስታዊ መብቱ የተከበረ መሆኑን ያስታወሱት ርዕሰ መስተዳድሩ በቀጣይም ከአማራ ክልል ወደ ክልላችን ለስራ በሚገቡበት ሁኔታ ላይ ስምምነት ላይ መደረሱን አመልክተዋል። ይሁን እንጂ የክልሉ ደን እንዳይወድምና ጥበቃ እንዲደረግ ከአማራ ክልል ጋር ከስምምነት ላይ ተደርሷል ብለዋል።

በትናንትናው ዕለት በፍኖተ ሰላም ከተማ ተፈናቃዮችን ወደመጡበት አካባቢ ለመመለስ 11 መኪኖች መዘጋጀታቸውንና ተፈናቃዮቹን የሚያጅቡ የፌዴራል ልዩ የፖሊስ ኃይል መታጀባቸውን የዓይን ምስክሮች ገልፀዋል።

********

Source: Sendek – April 10, 2013. Originally titled “ከቤንሻንጉል ክልል የተፈናቀሉ የአማራ ተወላጆች ወደነበሩበት እንዲመለሱ ተወሰነ”

Related (in this blog):

የቤንሻንጉል ተፈናቃዮች ተመፅዋች ሆኑ

የቤንሻንጉል ፕ/ት:  ተፈናቃዮቹ ኦሮሞዎችም ናቸው – አጣርተን እርምጃ እንወስዳለን

በቤንሻንጉል ክልል የሰፈሩ ዜጐች “ሕገወጥ” በሚል ተባረሩ

Content gathered and compiled from online and offline media by Hornaffairs staff based on relevance and interest to the Horn of Africa.

more recommended stories