ብዙ ጊዜና ገንዘብ ኣውጥቼ ሰራሁት ያለውንና “ፌዝ-ራሊዝም” ብሎ የሰየመውን ፊልም በኢሳት ቴሌቪዥን ጋብዞን ነበር፡፡ የትግራይ ተወላጆች የሆኑና በተለያዩ የፌዴራል መንግስትና የመከላከያ ሰራዊት ያሉ ሃላፊዎችን (ተጋሩ ያልሆኑትንም እየጨመረ) ስምና ምስል ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በመቅዳት ያሳየው ይሄ “የምርምር ግኝት” ማጠቃለያው ‘ኢትዮጵያ ውስጥ ፌዴራሊዝም የለም ፌዝ-ራሊዝም ነው ምክንያቱም ስልጣኑን የያዙት “ትግሬዎች” ናቸው የሚል ነው፡፡ በርግጥ እነ ታማኝ ስለ ፌዴራሊዝም ማውራት መጀመራቸው በራሱ ትልቅ ለውጥ ቢሆንም ፅንሰ ሃሳቡ የገባው ኣልመሰለኝም፡፡

ሰዎችን ማማት ወይም ማጣጣል ጥሩ ኣይደለም፡፡ ሆኖም የፖለቲካ ሰዎች የሚሉትንና የሚያደርጉትን መተቸት እና መቦጨቅ ኣንዱ የፖለቲካ ኣካል ነውና ኣንዳንድ ሰዎችን እንቦጭቅ፡፡ የቡጨቃው መነሻ የዲያስፖራ (የዲሲ) ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ነን ባዮች የኢትዮጵያ ፖለቲካን ኣስመልክቶ በቅርቡ ያደረጉትና የተናገሩትን ነው፡፡ የዲሲ ፖለቲከኞቻችን መተቸት በዲያስፖራው የተቃውሞ ፖለቲካ ህግ መሰረት ወንጀል ቢሆንም እስቲ ቡጨቃውን እንቀጥል…. !

የዛሬን ኣያርገውና ተስፋዬ ገብረኣብ ድሮ ኢህኣዴግ በነበረ ጊዜ የሚያዘጋጃት “እፎይታ” የምትባል ጋዜጣ ላይ ኣንዲት ኣጠር ያለች ኣምድ ነበረቸው ….. “ኣረፍ ይበሉ” የምትል፡፡ በዚህ ኣምዱ ተስፋዬ የኣሁኖቹ  የትግል ጓዶቹን-  እነ ሲሳይ ኣጌናን እና ሌሎች የግል ጋዜጣ ኣዘጋጆችና ፖለቲከኞችን መልሶ በብእር የሚወጋባትና የሚቦጭቅባት ገበታ ነበረች፡፡ እና እቺም ቡጨቃ በዛው እናስኪዳት፡፡ በነገራችን ላይ ተስፋዬ ገብረኣብን ካነሳን ኣይቀር ቡጨቃዉን በሱ እንጀምረው፡፡

ተስፋዬ በራሱ መፅሃፍ (የጋዜጠኛው ማስታወሻ) ላይ እንደነገረን ከሆነ ከደርግ ሰራዊት ጋር በፕሮፓጋንዳ ወታደርነት ተሰልፎ ወያኔን በሚዋጋበት ወቅት ደብረታቦር ላይ እንደተማረከና ወዲያውም የወያኔ ሃላፊዎችን ጠይቆ ከነሱ ጋር እንደተቀላቀለ ተርኮልናል፡፡ በዚህም መሰረት ተስፋዬ “በተማረከ በሰኣታት ውስጥ የወገን ጦርን እና ጓዶቹን መልሶ የወጋ ብቸኛ ኣፍሪካዊ ወታደር” የሚል ማእረግ ኣግኝቷል፡፡ ከዛም በኋላ ኢህኣዴግን ለኣመታት ኣገልግሎ ተፈላጊነቱ እየቀነሰ ሲሄድ በእረፍት ስም ኬንያ ሄዶ በዛው እንደቀረ በራሱ ብእር ኣውግቶናል፡፡ ከዛን ጊዜ ጀምሮም ኢህኣዴግን ሲያገለግሉ በነበሩት ጣቶቹ መልሶ ኢህኣዴግን መውጋት ቀጥሏል፡፡ ኣንዳንድ ሃሜተኞች እንደሚሉትም በተለይ ባለፉት ጥቂት ኣመታት ኣስመራ ድረስ እየተመላለሰ የሻእቢያን ጸረ-ኢትዮጵያ የፕሮፐጋንዳ ትእዛዞችን እየተቀበለ በተለያዩ ፅሁፎቹ ሲያንፀባርቃቸው ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ባለፉት ጥቂት ወራት ተስፋዬ ገ/ኣብ ከሚድያ ጠፍቷል – መጻፍም ኣቁሟል፡፡ የጠፋበት ጊዜም የኤርትራው የማስታወቂያ ሚኒስቴር የነበሩት ኣቶ ኣሊ ኣብዱ  ከተሰወሩ በኋላ መሆኑ ትንሽ ጥርጣሬ ያደረባቸው ኣንዳንድ ጠርጣሪዎች ኣንድ ነገር እንዲጠረጥሩ ኣድርጓቸዋል፡፡ ክንፈ የሚባል ኣንድ በህይወት የሌለ ሰው ነገረኝ ብሎ ኣንዱ ወሬኛ እንዳወራው ከሆነ ግን የተስፋዬ ኣለቃ የነበሩት ኣቶ ኣሊ መሆናቸውንና እሳቸው መንግስታቸውን ክደው ከተሰወሩ ወዲህ  ኣቶ ኢሳይያስ የኣሊ  ቦታ ላይ ሌላ ሰው እስኪተኩ ድረስ የተለመደው የፈጠራ ትረካ እየጻፈ እንደሆነ ነው፡፡ ምን ችግር ኣለው ደግሞ ቁጭ ብሎ ለመፃፍ … የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎችን የኑሮ ምንጭ በተመለከተ የኔዘርላንድ ግብር ከፋዮች ይጨነቁበት፡፡

*************************************

ታማኝ በየነ- እንደገና የዛሬን ኣያርገውና ድሮ ታማኝን የምናውቀው የደርግን ስርኣት በሚያገለግልበት ወቅት መድረክ ላይ ወጥቶ “ሂድ” “ግፋ በለው” እያለ ሲያቅራራ ነው – ይሄ ማለት ስራ ነበረው ማለት ነው፡፡ ከዛ በኋላ ግን ኣሜሪካን ኣገር ሄዶ በዲሲ ጎደናዎች ላይ የተቃውሞ ሰልፍ ሲደረጉ ከሚያሰማቸው መፎክሮችና በየስብሰባው ከሚያደርጋቸው ዲስኩሮች ውጪ ምንም ኣይነት ስራ እንደማይሰራ ሰለሞን ተካልኝን የመሳሰሉ የድሮ ጓዶቹ ይገልጻሉ፡፡ በዚህም መሰረት ታማኝ “ለሁለት ኣስርት ኣመታት ኣሜሪካን ኣገር ያለ ስራ የኖረ ብቸኛ ኢትዮጵያዊ” የሚል ማእረግ ሰጥተውታል፡፡ ኣሁን ግን ይሄ ኣይሰራም የሚለው ነገር ሰለቸው መሰለኝ ባለፉት ሳምንታት ብዙ ጊዜና ገንዘብ ኣውጥቼ ሰራሁት ያለውንና “ፌዝ-ራሊዝም” ብሎ የሰየመውን ፊልም በኢሳት ቴሌቪዥን ጋብዞን ነበር፡፡ የትግራይ ተወላጆች የሆኑና በተለያዩ የፌዴራል መንግስትና የመከላከያ ሰራዊት ያሉ ሃላፊዎችን (ተጋሩ ያልሆኑትንም እየጨመረ) ስምና ምስል ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በመቅዳት ያሳየው ይሄ “የምርምር ግኝት” ማጠቃለያው ‘ኢትዮጵያ ውስጥ ፌዴራሊዝም የለም ፌዝ-ራሊዝም ነው ምክንያቱም ስልጣኑን የያዙት “ትግሬዎች” ናቸው የሚል ነው፡፡ በርግጥ እነ ታማኝ ስለ ፌዴራሊዝም ማውራት መጀመራቸው በራሱ ትልቅ ለውጥ ቢሆንም ፅንሰ ሃሳቡ የገባው ኣልመሰለኝም፡፡ ታማኝ ትምህርት ኣቋርጦ የደርግን የፕሮፓጋንዳ ስርኣት ለማገልገል በገባበት ጊዜና ከዛም በኋላ የፌዴራሊዝም ፅንሰ ሃሳብ ስላልነበረው ኣይፈረድበትም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በኣሁኑ ሰኣት ክልሎች ከዛም ኣልፎ ወረዳዎችና የከተማ መስተዳድሮች ራሳቸውን የሚያስተዳድሩት ራሳቸው መሆናቸውንና የሚላክላቸው በጀትና የሚሰበስቡት ግብር ራሳቸው በምክርቤቶቻቸው ውሳኔ ወደ ፈለጉበት ሴክተር የሚያዉሉበት ያልተማከለ ኣሰራር ነው ያለው –  ፌዴራሊዝም ማለት ደግሞ ያ ነው፡፡ ታማኝ ሲሳተፍበት በነበረው ስርኣት እና ከዛ በፊት ከጎጥ ጀምሮ እስከ ላይ ያሉ ሃላፊዎች ከኣዲስ አበባ የሚላኩበት ዘመን ስለነበረ ኣሁንም በዛ መነፅር ቢያስብ ኣይፈረድበትም፡፡ ለመሆኑ ኣምስት የሚሆኑ ትግሬ ኣምዳሳደሮችን ስም ዘርዝሮ ፌዴራሊዝም የለም ያለን ግን ኢትዮጵያ በኣለም ሙሉ ምን ያህል ኣምባሳደሮች ቢኖሯት ነው?…. የተቀሩት ኣምባሳደሮችስ ከየት እንደሆኑ ቢነግረንም ጥሩ ነበር፡፡ ኣንዳንድ ኣማራ ነን ብለው የሚያስቡና የሚናገሩ እንደነ ኣምባሳደር ህላዌ ዮሴፍ የመሳሰሉትን የኢህኣዴግ ባለስልጣናት “ኣማራ” ኣይደሉም “ትግሬ” ናቸው ሲለን …. ሜ/ጄ/ ኣበባው ታደሰንም ኣማራ ናቸው ኣትበሉ ሰውዬው “ኣገውና ትግሬ ቅልቅል ናቸው” ብሎ ዘራቸውን ቆጥሮልናል፡፡ በነገራችን ላይ ታጋይ ታማኝ ቀለም ኣይወድም ኣሉ እንጂ “Genealogy” የሚባል የዘርና የዝምድና ቆጠራ የሚያጠና የትምህርት ዘርፍ ኣለ እሱን ቢያጠና ጥሩ ይዋጣለት ነበር፡፡

*************************************

በኢሳት ገንዘብ ከሚተዳደሩና ኑሯቸውን ከሚመሩ ሰዎች ኣንዱ ኣርበኛው ኣበበ ገላው ባለፉት ሳምንታት ቦስተን ላይ የተዘጋጀ “የኢሳት ገንዘብ ማሰባሰቢያ ዝግጅት” ላይ በእንግድነት ተገኝቶ ነበር፡፡ ያንን ሁሉ ርቀት ተጉዞ በኣዳራሹ ያገኘው ሰው ብዛት የሚያስተዛዝብ ቢሆንም ታሪካዊ የተባለለትን ንግግር ከማድረግ ግን ኣላገደዉም፡፡ በንግግሩም ለመግቢያ ያህል የኢሳትና የግንቦት7 የኣፍ መፍቻ ቋንቋ የሆነችውን የዘር ቆጠራና የትግራዮች ተጠቃሚነት ፖለቲካ ኣወራና ወደ ዋናው ጉዳዩ ገባ፡፡ እንዲህም ኣለ –

“ኢሳትና ጋዜጠኞቹ ብዙ ሰራ እየሰሩ ነው … ያለባቸው ችግር የገንዘብ ችግር ነው፡፡ ስለዚህ ገንዘብ መስጠት ኣለባችሁ ….  ኢሳት ዘለቄታዊ የሆነ እርዳታ ያስፈልገዋል፡፡ ወሳኝ ነው ብለን ደግሞ የምናምን ከሆነ ለገንዘባችን ልንሰስት ኣይገባም፡፡ ልንቆጥብ ኣይገባም፡፡ ገንዘባችንን ከቆጠብነው ውጤታማ ኣንሆንም፡፡ ባለን ከልባችን መስጠት ኣለብን (ብርርርርር) …. እንበልና እኔ ኣሁን በ May 18 ድምጼን ብቆጥበው ኖሮ ኣቶ መለስ እንኳን ሊደነግጡ ኣይሰሙኝም ነበር …. ስላልቆጠብኩ ነው” (ሳቅና ጭብጨባ)

…….  ኣለና በጣም ኣርበኛ እንደሆነ ሆኖም ግን ኣገሪቷን ነፃ የማውጣት ሃላፊነት የሱ ብቻ እንዳልሆነና ሌላውም ብር በመስጠት  እንዲሳተፍ ተማፀነ፡፡ ለ17 ኣመታት ያህል ደርግን ተፋልመው፣ በየቀኑ መድፍና የኣውሮፕላን ድብደባን ሲጋፈጡና ሲታገሉ ቆይተው ለድል የበቁት ኣቶ መለስ እንዴት ኣሜሪካ ውስጥ ከኦባማ ጎን ቁጭ ብለው በኣበበ ድምፅ ሊደነግጡ እንደሚች ኣልገባንም ፡፡ በስብሰባው ንግሩን ኣድምጠው ሲስቁና ሲያጨበጭቡ የነበሩ ሰዎች ግን ገርሟቸው ይሁን ደንቋቸው ኢሳት የዘገበው ነገር የለም፡፡ 

ከቦስተኑ ስብሰባ በኋላ የመጣችው “ኣበበ ላይ የተቃጣው የግድያ ሙከራ በ FBI ጣልቃገብነት ከሸፈ” የምትለዋ ቀልድ ደግሞ በጣም ታዝናናለች – ኣርበኛው ኣበበ “ንግግር በማደርግበት ሰኣት የFBI ሰዎች እየጠበቁኝ  ነበር  ብሎናል” :: ወይኔ ወጌሻው !  “የት ይደርሳል የተባለ ሙክት ቄራ ተገኘ” ኣሉ ኣባ ዱካው፡፡ ስንት ተዋግቶ ያዋጋናል ብለን “የኣመቱ ምርጥ ሰው” ኣድርገን የሾምነው “ኣርበኛችን” ለካ በኣሜሪካን ኣገር እየኖረ ‘ህወሓቶች ዛሬ ገደሉኝ ነገ ገደሉኝ’ በሚል ጭንቀት ውስጥ ነው ያለው፡፡ እኔን እኔን – እንደዚህ ኣይነት ጭንቀትስ ነብርን ያየች ሚዳቋ ትኑረው – ያቺ ድንጉጥ፡፡ ኣይዞህ ተባ ማለት ነው፡ማንኛውም በሚቀጥሉት ጥቂት ቀናት “ከህወሃት የግድያ ሙከራ ባመለጠው በጀግናው ኣበበ ገላው ስም የኢሳት ገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም” ወይ  ደግሞ “የዲያስፖራው ተቃዋሚ ሃይል ኣለኝ የሚለው የኣመቱ ምርጥ ጀግና ከነቤተሰቡ ደህንነታቸውን ለመጠበቅ የሚውል የብር ማሰባሰቢያ ፕሮግራም” የሚሉ የሚጢጤዋ “የግድያ ሙከራ” ድራማ ዋና ማሳረጊያ ዘመቻዎችን እንጠብቅ፡፡

 *************************************

ሰሞኑ ከሰማናቸው ነገሮች ኣንዱ “የግንቦት ሰባት ህዝባዊ ሃይል” የተባለ ተዋጊ ሃይል መቋቀዋሙን ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ትንታኔ የሰጠው የኢሳቱ ታጋይ ሲሳይ ኣጌና … ይሄ ሃይል ወያኔን ኣዲስ ኣበባ ድረስ ተሸክሞ ወስዶ ለስልጣን ያበቃ የሻእቢያ ድጋፍ ስላለው በቀላሉ ወያኔን ማሸነፍ እንደሚችል ግምቱን ሰጥቷል፡፡ በመቀጠልም በ199ዎቹ በኮንጎ (ዛየር) የሎረን ካቢላ ኣማፂ ሃይሎች የሞቡቱ ሴሴሴኮን መንግስት በ7 ወር ውስጥ መጣላቸውንና “ውጊያው የማራቶን ሩጫ ያህል ቀላል እንደነበረ” ፣ ኣሁንም የተቋቋመው ሃይል በተመሳሳይ ሁኔታ ወያኔን ሊጥል እንደሚችል ተንትኗል፡፡ ኣንዳንድ ሃሜተኞች ኣቶ ሲሳይን “ታዲያ እስከ ዛሬ ወያኔን ለመጣል የከበደን የማራቶን ሯጮች ስላልነበሩን ነው ወይ ?”  ብለው የጠየቁ ሲሆን “ሻእቢያ ወያኔን ጥሎ ሌሎችን ወደ ስልጣን ለማምጣት ኣቅም ካለው ምነው ትንሽዋ ባድሜ ላይ ጉልበት ኣጣ?  ሲሉ ኣክለዋል፡፡

*************************************

ዶክተር ብርሃኑ – “የግንቦት ሰባት ህዝባዊ ሃይል” ተቋቁሟል ተብሎ በተገለፀበት ጊዜ “ህዝባዊ ሃይሉ ከዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር ግንኙነት ይኑረው ኣይኑረው ኣይታወቅም” የምትል ኣረፍተ ነገር እየተነበበች ነበር፡፡ ከዛም ዶክተሩ የህዝቡን ስሜት ከሰሙ በኋላ ኢሳት ቴሌቪዥን ላይ ቀርበው “እኔ የለሁበትም” ትግሉን ግን እደግፈዋለሁ ብለዋል፡፡ ምነው ዶክተሩ ፈሩሳ?….. በእርግጥ ሁኔታውን ኣይተው በኋላ ምን ሊሉ እንደሚችሉ ኣይታወቅም – መገመት ግን ይቻላል፡፡ ከዚህ በፊትም እኮ “ጦርነት የፋራ ነው” ብለውን ኣምነናቸው ስናበቃ ኣሜሪካን ኣገር ሄደው “ወያኔን ለመጣል ጦርነት ኣስፈላጊ ነው” ብለውናል፡፡ እንደዚህ ኣይነት ጨዋታ ላይ የተካኑ እንደሆኑ በ1997 ምርጫ ጊዜ በኣንድ በኩል ከተቃዋዎች ጋር ሆነው “ምክር ቤት ኣንገባም” ሲሉ በሌላ በኩል ደግሞ በግል ኢህኣዴግ ጋር እየሄዱ ሲደራደሩ የሚያውቋቸው ይናገራሉ፡፡ ኣሁንም ከጉዳዩ እየሸሹ ያሉት ኣንዳንድ ሰዎች “ለምን እርስዎስ ጫካ ሄደው ኣይዋጉም” ብለው የሚጠይቋቸውን ጥያቄ ለመሸሽ እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡ ከዚህ በፊት  ‘እኔ የቤተሰብ ኣስተዳዳሪ ነኝ በዛ ላይ ከነጮች ጋር ያለንን ግኙነት እንዳይቋረጥ እዚሁ ኣሜሪካ ልቆይ’ ብለው የተወሰኑ ጓደኞቻቸውን ኣስመራ እንደላኩ ሲገለጽ ነበር፡፡ እንደዉም ይሄንን የሰሙ ኣንዳንድ የድርጅታቸው ቀልደኛ ኣባላት ዶክተሩን “ህወሃትን የመሩት እነ ኣቶ ኣባይ ፀሃዬ ኣቦይ ስብሃት መለስና ሌሎቹ የህወሃት ታጋዮቹን  እኛ እዚህ እንሁንና እናንተ ሂዱ ተዋጉ ኣላሉም – ራሳቸው ናቸው መጀመርያ በረሃ የገቡት፡፡ ባይሆን ከነጮች ጋር መገናኘት ካስፈለጋቸውም እነ ብርሃነ ገብረክርስቶስን ይልካሉ እንጂ በረሃን ጥለው ከተማ ኣይገቡም ነበር”  ብለዋቸዋል ኣሉ፡፡

*************************************

 ዶ/ር ፍስሃ እሸቱ – የዛሬን ኣያርገውና ዶ/ር ፍስሃ ድሮ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲን ኣቋቁመው ለሃገራቸው በተግባር የሚታይ ልማትና ኣስተዋፅኦ በማድረግ በበጎ ከሚነሱ ኢትዮጵያውያን ኣንዱ ነበሩ፡፡ ኣሁን የተመሰቃቀለውንና ግራ የገባውን የዲስፖራው የፖለቲካ ተቃውሞ ተቀላቅለው ኣንዴ ‘በ6 ወር ኢትዮጵያ ውስጥ ለውጥ ሊመጣ ነው የሽግግርመንግስት እናቋቁም’ ሲሉን ሌላ ጊዜ ‘በህልም የተገለጸልኝ የድል ሚስጥር ኣለ’ ሲሉን ቆይተዋል፡፡ ሰሞኑን ደግሞ “ኣውራ የሌለው ትግል እረኛ የሌለው መንጋ ነው – እኔ መሪዬን መርጫለሁ እናንተስ ? በሚል ጽሁፋቸው ያለፉት 21 ኣመታት የኢትዮጵያ ጉዞና ኣሁን ያለችበት ደረጃ በጥልቀት በመዳሰስ ደረስኩበት ያሉትን ግኝትና በዛም መሰረት ኣዳበርኩት ያሉትን አዲስ ሀሳብ (thesis) ይዤ መጥቼኣለሁ እንካችሁ ብለዋለ፡፡ ዶክተሩ ኣዲሱን ሃሳብ ሲያብራሩ እንዲህ ብለዋል፡፡

መሪ እፈልጋለሁ። የራሴን ኢትዮጵያዊ ማንዴላ እፈልጋለሁ። አስተባባሪ፤ መካሪ፤ አቅጣጫ ጠቋሚ፤ አስታራቂ፤ የተስፋ፤ የአላማና የኢትዮጵያዊነት ምልክት። ወያኔ ሟቹን መሪያቸዉን ታላቁ መሪ ብለዉ እንዳመለኩት፤ እኔም የኔ የምለዉ መሪ እፈልጋለሁ” ……. “ከዚህ አንጻር በኔ ፍፁም የማያወላዉል እምነትም ተበታትኖ ያለዉን የትግል ጎራ አሰባሳቢ ሊሆን የሚችል መሪ ከጀግናዉ እስክንድር ነጋ የተሻለ የኛ የዘመናችንና የራሳችን ማንዴላ ይኖራል ብዬ አላምንም”

ጉድ በል ጎንደር ኣለ ያገሬ ሰው፡፡ እስክንድር ድሃውንና ከሁለት ሶስተኛ በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚኖርበትን የገጠሩን ኣካባቢ ምን ያህል እንደሚያውቀውና እንደሚረዳው ባላውቅም ዶ/ር ፍስሃ ኣዲስ ኣስተሳሰብ (thesis) ኣዳበርኩኝ ሲሉን የጠበቅኩት ነገር ኣዲስ የፖለቲካ ወይም የልማት ኣስተሳሰብ ነበር – ለምሳሌ የኣቶ መለስ ኣስተሳሰብ ነው ተብሎ የሚነገርለትና ኢህኣዴግ የሚከተለው የፖለቲካና የተለየ የልማትና የእድገት ኣቅጣጫን የሚተካ ኣዲስ ኣስተሳሰብ ፡፡ ዶ/ር ፍስሃ ላመኑበት ኣላማ መታገላቸውን ኣደንቃለሁ ሆኖም ግን ነገረ ስራቸው ሁሉ ኣድሮ ቃሪያ መሆኑ ያሳዝናል፡፡ ለነገሩ “ከኣህያ ጋር የዋለች ላም ምን ትማራለች” ተብሎ የለ ?

**************

Please check the archives for more on the issues raised above.

* This article is part of the “Post-Meles 2012″ Special Edition of this blog.

Jossy Romanat

more recommended stories